Svoboda | Graniru | BBC Russia | Golosameriki | Facebook

በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ረሃብ በአፍሪካ

 የማላዊው ገበሬ በበቆሎ ማሳቸው ውስጥ ሲዘዋወሩ ዋና ከተማዋ አካባቢ ሊሎንግዌ፣ ማላዊ
የማላዊው ገበሬ በበቆሎ ማሳቸው ውስጥ ሲዘዋወሩ ዋና ከተማዋ አካባቢ ሊሎንግዌ፣ ማላዊ

በተፈጥሮ የሚከሰተው ኤልኒኞ፣ በፓስፊክ ምሥራቃዊ ውቅያኖስ አካባቢ ከሚታየው ያልተለመደ የውሃ ግለት የሚነሳው ሙቅ አየር በዓለም ዙሪያ የአማካይ ሙቀት መጠን እንዲጨምር በማድረጉ እና እንዲሁም ወደ ከባቢ ዓየር የሚለቀቀው በካይ የካርቦን መጠን የከሰቷቸው ሁኔታዎች ተደራርበው ድፍን ደቡባዊ አፍሪቃ ባለፉት ዓመታት አጋጥሞት በማያውቅ አስከፊ ድርቅ እየተናጠ ይገኛል። ይህንንም ተከትሎ ማላዊ፣ ዝምባብዌ እና ዛምቢያ ባለፈው ወር አከባቢውን በመታው ድርቅ ሳቢያ የአስቸኳይ ጊዜ አውጀዋል።

የምግብ አቅርቦት ምንጮች እየነጠፉ ባሉባት ማላዊ፡ የማሳ ሰብል ስርቆት ብርቱ ችግር እየሆነ ነው። የበቆሎ አምራች የነበሩ ኡላሊያ ላፑሶኒ የተባሉ አንዲት ገበሬ ሲናገሩ፡ በድርቁ ሳቢያ የዘሩት በቆሎ ባለማፍራቱ በአሁኑ ወቅት የረሃብ አደጋ ተጋርጦባቸዋል።

"እስኪ አስቡት ለዚህ ወር የሚሆን ምግብ የለንም፤ እንዴ አድርገን ተርፈን እስከሚቀጥለው ዓመት ተመሳሳይ ጊዜ መድረስ እንችላለን? ከባድ ነው የሚሆነው” ብለዋል የደረቀ ማሳቸውን እያሳዩ።

ከዚሁ በተያያዘም፡ የማላዊው ፕሬዝዳንት ላዛረስ ቻክዌራ ሃገራቸውን ከረሃብ አደጋ ለመታደግ አለም አቀፍ ለጋሾች እጃቸውን እንዲዘረጉ ጠይቀዋል። በዓለም ዙሪያ በ2023 አዲስ ሪከርድ ያስመዘገበው የአየር ንብረት ለውጥ ኤልኒኞ የሚያሳድረውን ተፅእኖ ማባባሱም ተዘግቧል።

ዓለም አቀፉ የረድኤት ድርጅት ኦክስፋም ባለፈው ሳምንት እንዳስጠነቀቀው፡ በደቡባዊ አፍሪቃ ከ24 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በድርቅ ሳቢያ ለረሃብ፣ የተመጣጠነ ምግብ እና የውሃ እጥረ ተጋልጠዋል።

በማላዊ በተከሰተው ድርቅ ሳቢያም ‘ዘጠኝ ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች ተጎድተዋል’ ሲል ዩኒሴፍ አስታውቋል።

ተመድ በኢትዮጵያ ለተረጂዎች ርዳታ ለማቅረብ የ998 ሚሊየን በጀት ክፍተት እንዳለበት አስታወቀ
please wait

No media source currently available

0:00 0:01:56 0:00

የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ (ኦቻ) ትላንት ባወጣው መግለጫ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ እስከ መስከረም ወር ባለው ጊዜ አስቸኳይ ርዳታ ያስፈልጋቸዋል ተብለው ከሚገመቱ ዘጠኝ ሚሊየን ተረጂዎች ውስጥ አምስት ሚሊየን ለሚሆኑት ብቻ የገንዘብ ድጋፍ ማግኘቱን እና ለቀሪዎቹ አራት ሚሊየን ተረጂዎች ተጨማሪ 998 ሚሊየን ዶላር እንደሚያስፈልገው አስታውቋል።

ኢትዮጵያ ውስጥ በቀጠሉ ግጭቶች እና ድርቅን እና ጎርፍን ጨምሮ የአየር ንብረት አደጋዎች አሉታዊ ተፅእኖ ምክንያት ኢትዮጵያ ውስጥ የምግብ ዋስትና እጦት እንዲባባስ በማድረጋቸው፣ እ.አ.አ በ2024 ከመጋቢት እስከ መስከረም ባለው ወር 9 ሚሊየን ሰዎች አስቸኳይ ርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው የመንግሥታቱ ድርጅት የሰብአዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ (ኦቻ) በትላንቱ መግለጫው አስታውቋል።

ከነዚህ ውስጥ በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በወር አምስት ሚሊየን ለሚሆኑ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች እና የምግብ ዋስትና የሌላቸው ሰዎች አስቸኳይ የምግብ ርዳታ ማድረግ የሚያስችል ድጋፍ ማግኘት ቢቻልም፣ በወር 4 ሚሊየን ለሚሆኑ ሰዎች የሚያስፈልገውን ወደ 468 ሺህ ሜትሪክ ቶን የሚጠጋ ምግብ ለማከፋፈል፣ የሰብል ምርትን ለመደገፍ፣ የውሃ አቅርቦት ለማሻሻል፣ ለጤና፣ ለትምህርት እና ለመሳሰሉት የበጀት እጥረት እንደገጠመው አመልክቷል።

ድርጅቱ ለተረጂዎቹ የሚፈለገውን ወደ 414 ሺህ የሚጠጋ እህል፣ ከ42 ሺህ በላይ ጥራጥሬ እና ከ12 ሺህ ሜትሪክ ቶን በላይ የአትክልት ዘይት ለማከፋፈል ወደ 475 ሚሊየን ዶላር የሚጠጋ ተጨማሪ በጀት ጠይቋል።

ከሚያስፈልገው ርዳታ ውስጥ የተገኘው ግማሽ ለሆኑት ብቻ መሆኑ አሳሳቢ ክፍተት መፍጠሩን የጠቀሰው መግለጫው፣ "ድጋፉ ካልተገኘ ተጋላጭ የሆኑት የኅብረተሰብ ክፍሎች እና የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች አደገኛ ወደሆነ የምግብ እጦት እንደሚገቡ" አመልክቷል።

በከፍተኛ የሰብአዊ ቀውስ ነች ለተባለችው ኢትዮጵያ እኤአ በ2024 በመንግሥቱና አጋሮቹ የታለመው ጠቅላላው የሰብአዊ ምላሽ እቅድ 3.237 ቢሊዮን ዶላር የሚጠይቅ ሲሆን፣ ይህ 15 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን ለመደገፍ ያለመ መሆኑ ተገልጿል፡፡

ድጋፉ የተመጣጠነ ምግብ እጥረትን ለመከላከል፣ ንፁህ ውሃና የንፅህና አቅርቦትን ለማረጋገጥ፣ የጤና አገልግሎት ለመስጠት፣ ትምህርትን ለመደገፍ እና የእንስሳት እርባታና የሰብል ምርት ድጋፎችን ለማሟላት የሚደረገውን ጥረት እንደሚያጠናክር በመግለጫው ተብራርቷል፡፡

ዝርዝሩን ከተያያዘው ፋይል ይከታተሉ።

ተጨማሪ ይጫኑ

XS
SM
MD
LG